Wednesday, February 22, 2012

እውነትን በዱላ


እንግዳ ባልሆንባቸው የኢሕአዴግ አምባገነነናዊ አገዛዝ ሥር ላለፉት ሃያ ዓመታት የተለያዩ የግፍና የጭቆና ሕይወትን አሳልፈናል ፤ ዕድሜና ጤናዉን ይስጠን እንጂ ገና ለሚቀጥሉት ሃያ ዓመታት ደግሞ‹‹ እንዲህ እንዲህ እያልን አብረን እንዘልቃለን፡፡››(ይህን ቃል ከኢትዮጵያ ሬድዮ የተዋስኩ ሲሆን ባለማስፈቀዴ በኮፒ ራይት መብት ጥሰት እንደማልቀጣ ተስፋ አለኝ ፡፡) አንተ ማን ነህና ነው የማትቀጣው እንደምትሉኝ ልመንና መልስ ልስጥ፡፡
 
ጫንቃችን  ላይ ያለው መንግስት የሚያስተዳድረን የተለያዩ ሃገራትን ልምድና ተሞክሮ በመቅዳት ፤ ያውም ለእኛ የሚበጀንን ብቻ አውጥቶና አውርዶ ከዓመት ዓመት ችግሮችን ሊቀርፍ የሚችል ህግና ደንብ በልካችን መትሮና ሰፍቶ ያለብሰናል፡፡ይህ ደግሞ መንግስት ሊያደርገው ከሚገባው አስተዳደራዊ ሥራ በጣም የትንሽ ትንሹ ነው፡፡ በመሆኑም በብቸችነት ከምሰማውና ራሱን በቴክኖሎጂና በሰለጠነ የሰው ሃይል ከማሳደግ ወደ ኃላ ብሎ የማያውቀው የፕሮፓጋንዳ ቋት የሆነው ሚዲያ እኔ ትዝ አልለውም ምክንያቱም ብዙ የሚሰሩ የቤት ሥራዎች አንዳሉበት ለፋፊ አያስፈልገንም ሁላችንም የምንጋራው ስለሆነ ማለቴ ነው፡፡ 
በዚህ ሁለት ቀናት ውስጥ የሰማናቸው ዜናዎች የሁሉንም ጆሮና አይን ቀጥ እንዲል ያደረጉ ናቸው፡፡የጋሽ ስብሃት ለአብ ገብረ እግዚአብሔር ሞትና እና በአቶ አንዱዓለም አራጌ ላይ የተቃጣው  ድብደባ በፖለቲካው ጎራና ከዚህ ጽንፍ ርቀው ያሉትን ኢትዮጵያውን አንድ መንፈስ የደመረ የሃዘን ቀናት ናቸው፡፡የሚፈልገውን ሆኖና አድርጎ ያለፈው ጋሽ ስብሃት ጽፎልን ባነበብናቸው መጻሕቶቹ ስቀን፤ተቆጥተን፤አንዳንዴም ባሕላችን አረከሰው ብለን አንጃ ለይተን ተከራክረን አልፈናል፡፡ጋሼም ዶማን ዶማ እንጂ ማሻሻያ ቋንቋ እየፈለጉ እውነትን መደበቅ እንደማይኖርብን ሞግቶ ጽሁፉን እንደወረደ አሳትሞታል፡፡ነፍስ ይማር፡፡
ሌላው ወጣቱ ፖለቲከኛ አንዱዓለም አራጌ የዕድሜ ልክ እስረኛ በሆነ ‹‹ታራሚ›› የደረሰበት ከፍተኛ ድብደባ ለሕይወቱ አስጊ መሆኑን፤ወደ ህክምና ተቋም ለመሄድ ስጋት እንደገባው፤መንግስትም ሆነ ብሎ እውነት በዱላ ለማፈን እያደረገ ካለው እንቅስቃሴዎች አንዱ ማሳያ ነው፡፡አንዱአለም በሚያራምደው ፖለቲካዊ አቋም እየደረሰበት ያለው ድብደባ ይህ የመጀመሪያው ሳይሆን ከ1997 ዓ.ም  እስከ ታሰረበት ጊዜ የተለያዩ ክትትሎች፤ ዛቻና ማስፈራራት ሲደርስበት ቆይቷል፡፡ይህ በአንዱዓለምና በሌሎች የፖለቲካ አጋሮቹ ላይ የተቃጣው የውንብድና ሥራ የወያኔ የ37 ዓመታት መክሊታዊ መገለጫዎቹ ናቸው፡፡ለዘመናት እንዳየነውና ከመጻሕፍት እንዳነበብነው አምባነናዊ መንግስታት ሲያልፉ ሃገርና እውነት ግን ቋሚ ናቸው፡፡እውነት በዱላ የምትሸፈን ሳትሆን እያደር እየፈካች የምትሄድ ቀይ ኮከብ ነች፡፡
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር፡፡

Wednesday, February 15, 2012

‹የምርጦች ምርጥ አዋጅ››የሽብርተኝነት አዋጅ

 
ከትናንት ወዲያ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተገኝተው የሃገሪቱን የስድስት ወር ሪፖርት አቅርበው ነበር፡፡እኔም ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግሮች የታዘብኩትን ላካፍላችሁ ወደድኩ፡፡
ዘወትር ፌዝ የማይለው የሃገራች ምክር ቤት ዛሬም የህዝቡን ብሶትና ሮሮ እንደመስማት የተጻፈላቸውን እና የታዘዙትን እንዲጠይቁ በማድረግ በትውልድ ላይ ዛሬም መቀለዳቸውን ቀጥለዋል፡፡ኢትዮጵያየ ለዚህ በቃሽ ?‹‹ሃገር ሲያረጅ ጃርት ያበቅላል፡፡››ይሉ ነበር አባቶቻችን፡፡ይኸው ዛሬ በእኛ ዕድሜ አየነው የመከራ ገፈት ቀማሽ ፤የችግር ተቐዳሽ ሆንን፡፡ይባስ ብሎም ግብር ከፍለን ባቆምነው ሚዲያ ሃያ ኣመታች እየተሰድብን አለን፡፡ድሮም በእብሪት የተሞላ ሕሊና ከሆዱ ባለፈ ለሃገርና ለወገን የማሰብ እንጥፍጣፊ መልካም እሳቤ ያልፈጠረበት የዘመናችን ጉድ i
ጆሮ አይሰማው የለ የሽብርተኝነት አዋጁ ከብዙ ሀገራት የተቀዳ /የተኮረጀ/ የምርጦች ምርጥ አዋጅ ነው ሲሉ ያንቆለጳጵሱታል፡፡እኔ ምለው ግን ይች ሃገር ከውጭ የሚገባ እንጂ እዚሁ እኛ ሃገር የሚሰራበት በጎ ተሞክሮ የለም ማለት ነው ? የነጮቹ ህግ ብቻ ነው የእኛን ሃገር ፖለቲካ መፍትሄ የሚሰጠው እንዴ? ለነገሩ ምን ታደርግ ፤ከማንስ ትማር አባትህ ያወረሱህ ነው ይዘህ ያደግከው፡፡ድሮም የባንዳ ልጅ ባንዳ ነው፡፡ዘር ከምን ይስባል አይደል ትረቱስ፡፡
ምነው ታዲያ አፋኝ አፋኙን ብቻ መምረጥዎ? ነጮቹ እኮ ብዙ የብዙ ብዙ ዲሞክራሲያዊ የፖለቲካ ምህዳር አላቸው እንደኮራጅ እሱንም አብሮ መሞጭለፍ ነበር እንጂ አንዱን ያዝ ሌላውን ለቀቅ ቂልነት ነው፡፡በሌላው የኩረጃ ስምሪት ጊዜ ግን አደራ አደራ እንዳይረሳ ፡፡ሌላው ጥሩ አማራጭ ደግሞ ቻይና ያሉት ልጆቻችሁን ነጻ የምርጫ ስነ-ምህዳር፤ነጻ ሚዲያ ሽፋን ፤የመሰብሰብ፤ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ፤የሰብአዊ መብቶችን የማክበር--------ዘዴን ባሉበት political boarding school የስነ ምግባር መመሪያ ሆኖ ቢሰጣቸው ወደ አባት ሃገራቸው ሲመለሱ ግር እንዳይላቸው ስለሚያደርጋቸው ቢታሰብበት መልካም ነው፡፡በተለይ ጨዋው የኢትዮጵያ ህዝብ ‹‹ሺህ ዓመት ይንገሱ››ብሎ እጅ ሲነሳ (ጣት ሲቆርጥ አላልኩም) እነሱም ለክብሩ የሚመጥን ዉዳሴ ህዝብ እንደሚያቀርቡ አምናለሁ፡፡
የተከበሩ ጠቅላይ ሚኒስትራችን እባክዎትን አሁንም ምርጥ ምርጥ ተሞክሮዎችን ወደ ሃገር ቤት Import በማድረግ የአባትዎትን ሃገር በባዕዳን ተሞክሮ ወደፊት ያራምዱ------------፡፡
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር፡፡

ኑሮ እና ሮሮ

 
ዕለቱ ቅዳሜ ነው፡፡ካሳለፍት ጊዜያት በተለየ ራሴን እንድፈትሽ አጋጣሚ የፈጠረ ዕለት፡፡በህሊና ከራሳችሁ ጋር ተማከሩ የለ ? እኔም ከዘወትሩ በተለየ ሁኔታጥልቅ ሃሳብ ገበቶኛል፡፡የወገኔ ኑሮ እና ሮሮ፡፡
በታከሲ ውስጥ ፤በየመስሪያ ቤቱ፤በየዩኒቨርሲቲው ግድግዳና መጸዳጃ ቤት የሚጻፉት ወጎች ቀልቤን ስበውታል፡፡ደርሶ ዛሬ ለምን በተለየ መልኩ ትኩረት እንደሰጠሁት አልገባኝም፡፡ለወትሮው ለዘብተኛ (ሊበራል) ከሚባሉት ወገን ነህ ይለኝ ነበር ባልንጀሮቼ፡፡ምንም አይገድህም …..ሀገር ብትለማም ብትጠፋም አንተ ሁድህ ከሞላ የሌላው ማጀት ትዝ አይልህም ሲሉ አሽሙር መናገራቸው ነው በእነሱ ቤት iii
እስኪማን ይሙት…….. ? አሁን በሀገራችን ምን ጠፍቶ ነው ? ርሃብ፤ የኑሮ ውድነት ……ወዘተ የሚባለው ?
በዚያ ሰሞን የተከበሩ ጠቅላይ ሚስትራችን ያሉትን አልሰማችሁም ማለት ነው እንዴ ? በሞቴ ላፍታ ላስታውሳችህ ‹‹በሃገራችን ችጋር እንጂ ርሃብ የለም››አይደለም ያሉት ? ታዲያ ከዚህ በላይ ማረጋገጫ ከየት ሊመጣ ነው ወዳጆቼ ?
በተከታታይ አምስት ዓመታት 11.5 በመቶ እድገት አሳይተናል፡፡ይህ ፈጣን እድገታችን አንዳንድ ጸረ -ልማት ሃይሎች ለማደናቀፍ ቢሞክሩም በህብረተሰቡ ትብብርና በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ክትትልና ርብርብ እድገታችንን በፈጣን ሁኔታ ማስቀጠል ችለናል፡፡ ደግሞስ በየመጠጥ ቤቱ እና ስጋ ቤቱ የሚቀርበውን የመጠጥ እና የቁርጥ አይነት ‹‹ያያና ተመገበ››ይፍረደኝ፡፡የኢኮኖሚያችንን እድገት ፖል ቴርጋት እንኮዋ አድቫንስ ሰጥተነው አይደርስብንም፡፡ታዲያ አንዳንድ አይናቸውና ጆሮአቸው ክፉ ክፉው ብቻ የሚስመለክታቸውና የሚያሰማቸው ርሃብ፤ የኑሮ ውድነት ፤የስራ እጦት ቅብጥርሴ ያስለፈልፋቸዋል ፡፡ ይህ የቅናት ዛር ካልሆነ ምን ሊሆን ይችላል? አንድ ኪሎ ስጋ 110 ብር እኮ እኛ ሃገር ነው አዎ የሚሸጠው በሞቴ ውጭ ያለ ወዳጅ ወይም ዘመድ ካለ በዚህ ብር ምን ሊገዛበት እንደሚችል ጠይቁት እና መልሱን ጻፉልኝ፡፡በእግጠኝነት አንድ በርገር እንç የመግዛት አቅም እንደለለው አስረግጦ እንደሚነግራችሁ ተስፋ አለኝ ፋሽስታዊ ስርዓት ካልሆነ በቀር፡፡
ደግሞ 2.4 ትሪሊዮን ብር ከሃገር ሸሸ እያሉ የሚያወሩ አሉ አሉ ? የምእራባውያን ሚዲያ እኮ ሃገሪቱ ብትፈርስ ደስታቸው ነው፡፡ቀን ከሌት እየሰሩበት ያለውም ርዕሰ ጉዳይ ኢትዮጽያና ኢትዮጽያዊነት ላይ ብቻ ሆኖአል፡፡አንዳንድ ጊዜም ከእኛዎቹ ሚዲያዎች በይዘትም በጥራትም ይበልጣሉ ሲሉ የሚከራከሩ ቢኖሩም እኛ ለወጣቶቻችን የምናስብላቸውን ቅንጣት ለጫትና ለሲጋራ የማይሸፍን ተቅዋም ይዞ መንቀሳቀስ የትም አያደርስም እኛ እኮ በዘፈን(ሙዚቃ ) ፤ሀሽሽና ጫት በገፍ ከየቦታው በማስመጣት አደገኛ ቦዘኔ እንዳሆንብን አጥብቀን እንሰራለን፡፡‹‹ለተቀናጀ የማደንዘዝ አጀንዳ እንሰራለን››አይደል ‹‹እኛ ሚዲያዎችስ›› የሚሉት፡፡
እናም ወገኔ ፈረንጆቹ በወረፋ ምግብ መታደል ሲጀምሩ እኛ ደግሞ በምግብ ራሳችንን ስንችልና በቀን ሶስት ጊዜ በልቶ የሚያድር አርሶ አደርና አርብቶ አደር ባፈራንበት በዚህ ወቅት ሃገራችንን በሲኦል ደጅ ባትመስሉብን ጥሩ ነው፤ቢያንስ ቢያንስ ለገጽታችን፡፡አንዳንድ ጀግና የልማት ሰራዊት አባላት ቤታቸውን በቆርቆሮ ፤ አጥራቸውን በግንብ፤ኑሮአቸውን(በርሃብ አላልኩም እንዳትሳሳቱ) በምቾት ባደረጉበት በዚህ ወቅት አመድ ለመነስነስ የሚደረገው ሩጫ ለማንም የሚበጅ አይደለም፡፡በመሆኑም የእኔን ምክር ስሙኝ እባካችሁ እረፉና ርሃባችሁን አስታሙ፡፡ያለን ይበቃናል!!! ሌላ ርሃብ፤ ችጋር……..እንዳይመጣብን ስለኑሮ ሮሮ አታሰሙን ፡፡
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር፡፡